19/01/2022
ኢትዮሪካ, [4/19/2021 12:50 PM]
ጸጋዬ ገ/መድኅን፣ እውቅ የቴያትርና የሥነጽሑፍ ሰው
ደራሲ ጸጋዬ ገ/መድኅን ነሐሴ 10 ቀን 1928 ዓ.ም በሐገረ ሕይወት መወለዱንና እዚያውም እስከ ስምንተኛ ክፍል መማሩን፣ ከንግድ ሥራ ትምህርት ቤት ከተመረቀ በኋላም በ1952 ዓ.ም ቺካጎ ከሚገኘው ብላክስቶን ከፍተኛ ትምህርት ቤት የሕግ ዲግሪ መቀበሉን፣ በእንግሊዙ የዊንደርስ ሮያልና በለንደኑ የብሪቲሽ ሮያል ቴያትር በመገኘትም የእንግሊዝን የቴያትር አሠራር መለማመዱን፣ በመቀጠልም የፈረንሳይን ብሔራዊ ቴያትርና የሮምን ኦፔራ ማጥናቱን በታዋቂው የስፖርት ጋዜጠኛ ሰለሞን ተሰማ የሚዘጋጀው "አስደሳቾቻችንን እንወቃቸው" የተሰኘ መጽሔት በ1957 እትሙ (ገጽ 23-25) አትቷል።
ደራሲ ጸጋዬ በርከት ያሉ ድርሰቶችን የጻፈና ከውጪም የተረጎመ ሲሆን የኢትዮጵያ የቴያትር ታሪክ በግንባር ቀደምትነት ከሚያነሳቸው ዋና ዋና ጠቢባን አንዱም ነው። ከወጥ (ኦሪጅናል) ሥራዎቹ የሾህ አክሊልን፣ በልግን፣ ሀሁ በስድስት ወርን፣ እናት ዓለም ጠኑን (በቤርቶልት ብሬሽት "ማዘር ከሬጅ" ላይ ተመሥርቶ የጻፈው ነው)፣ አቡጊዳ ቀይሶን፣ መልዕክተ ወዛደርን፣ ጴጥሮስ ያቺን ሰዓትን፣ ቴዎድሮስን፣ ምኒልክን፤ ከትርጉም ሥራዎቹ ደግሞ ኦቴሎን፣ ሐምሌትንና ማክቤዝን ከሼክሲፒር፣ ታርቲዩፍንና የፌዝ ዶክተርን ከሞልዬር መጥቀስ ይቻላል። "እሳት ወይ አበባ" የተሰኘ የስነግጥም መድበሉም ዘመን የማይሽራቸው ግጥሞቹን የያዘ ነው።
ደራሲ ጸጋዬ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን ሽልማት በሥነጽሑፍ መስክ የተቀበለ ሲሆን በደርግ ዘመንም በባህል ሚኒስቴር ቋሚ ተጠሪነት፣ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴያትር አስተዳዳሪነትና በአማካሪነት አገልግሏል። በገጠመው የጤና እክል ምክንያት በአሜሪካ ሕይወቱ እስካለፈበት ጊዜ ድረስም ብዕራዊ ተጋድሎውን አላቆመም ነበር። ከዚህ በተጨማሪ የሕይወት ታሪኩን ፋሲል ይትባረክ የተባለ ደራሲ እንዲጽፍ ተስማምተው ቃለመጠይቅ እያደረገለት ነበር። ሆኖም ሥራው ገና ዳር ሳይደርስ ታላቁ ባለቅኔና ፀሐፌ ተውኔት በድንገት አልፏል። ደራሲ ፋሲል ግን የጀመረውንና የባለቅኔውን ሥራና ህይወት የሚያስተዋውቀውን መጽሐፍ እንደ ፈረንጆቹ አቆጣጠር በ2013 ለማጠናቀቅ ችሏል። በዚህም የባለቅኔውን አስተዳደግና የሕይወት ጉዞ ቃኝቷል። ያ ሁሌም ስናዬው በሸሚዝ ላይ ሰደሪያ፣ በሰደሪያ ላይ ኮት፣ በዚያ ላይ ካፖርት፣ አንገቱ ላይ ስካርፍ፣ አናቱ ላይ ደግሞ ባርኔጣ የማይለየው ባለቅኔ፣ ትናንት እንደሁላችን ወጣት የነበር መሆኑን ያስታውሰናል። የፈጠራ ሥራዎቹን ለመተንተንና ለማስተዋወቅ ከፍተኛ ጥረት አድርጓል። የባለቅኔውን ድምፅና ቃና እንዲሁም ሰብዓዊ መለያዎችና ባህሪይም ይዞ ለመዝለቅ ችሏል። ለዚህም በጣም ልናመሰግነው ይገባል። ቀጥሎ የምናሰማችሁ ታሪክም ይኸው "Soaring on Winged Verse: The Life of Ethiopian Poet-Playwright Tsegaye Gebremedhin" በሚል ርዕስ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተዘጋጀው መጽሐፍ በተመረቀበት ወቅት በቀጥታ ትርጉም ሳይሆን የታላቁን ደራሲ የተለያዩ ገጠመኞች፣ በተለይም ከድርሰት ህይወቱ ጋር የተያያዙትን፣ ለታዳሚዎቹ ለማስተዋወቅ ያደረግኩትን አጭር ሙከራ ነው።
የጸጋዬ ገ/መድኅን ልጅነትና የፈጠራ ሥራዎቹ ጅማሬ
የአጼ ኃይለ ሥላሴ የአምቦ ጉብኝት ወጣቱ ጸጋዬ የሚማርበትን የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤትም ያጠቃልል ነበር። ስለዚህም መላኩና ዴሬሳ የተባሉ የትምህርት ቤት ጓደኞቹን አስተባብሮ፣ ማታ ራታቸውን አብልቶ፣ እርጎ አጠጥቶ፣ ሌሊቱን ሙሉ ቴያትር ሲያስጠናቸው ሊያድር ወስኗል። የስድስተኛ ክፍል የእንግሊዝኛ መጽሐፋቸው ጸጋዬ የሚወደውን King Dionysius and His Two Brothers (ንጉሥ ዳዮኒስስና ሁለት ወንድሞቹ) የተሰኘውን ተውኔት የያዘ ነው። ደጋግሞ አንብቦታል፣ ስለዚህም ብዙውን ክፍል በቃሉ አጥንቶታል። እናም ለጃንሆይ የሚቀርብ ከዚህ ጥንታዊ የግሪክ ተውኔት የበለጠ ስጦታ እንደማይኖር ገምቷል። ከዚያም ጓደኞቹን፣
"የንጉሥ ዳዮኒስስን ቴያትር እንለማመዳለን" ይላቸዋል።
"ለምን?" ዴሬሳ ነበር።
"ለጃንሆይ እናሳያለን"
አፋቸው በእርጎ የተሞላው ሁለቱ ልጆች መገረማቸው አልቀረም።
"ይኸን ሁሉ ባንድ ቀን ልናጠናው አንችልም፣ ብዙ ጊዜ የሚጠይቅ ነገር ነው።" መላኩ ተቃወመ።
"እንችላለን፣ ታያላችሁ። እንሞክረው" ጸጋዬ በሃሳቡ ገፋበት።
"ቀድሞ ነገር ለጃንሆይ እንድናሳይ አይፈቅዱልንም። ኧረ አጠገባቸውም አያስደርሱን" አለ ዴሬሳ።
"ግድ የለህም፣ ለእንግሊዝኛ አስተማሪያችን ለሚስዝ ሃቺንግስ እንነግራታለን። እሷ ደግሞ ለዲሬክተሩ፣ ለባለቤቷ ማለት ነው፣ ትነግርልናለች። ዲሬክተሩ ከፈለገ ሊረዳን ይችላል። ... ዴሬሳ፣ አንተ ትልቁን ወንድም ትሆናለህ። መላኩ ታናሽዬውን። እኔ ንጉሡን።" ጸጋዬ የሚበገር አልሆነም።
ከዚያ ሥራቸውን ቀጠሉ። ትልቁ ሸክም በጸጋዬ ትከሻ ላይ መውደቁ አልቀረም። በማግስቱ፣
"ጓደኞቼና እኔ እጃንሆይ ፊት የሚቀርብ ቴያትር አዘጋጅተናል።" ሲል ሃሳቡን በሚስዝ ሃቺንግስ ክፍል ውስጥ ይፋ አደረገ።
"የምን ቴያትር ነው ጸጋዬ?" ሃሳቡን ነገራት።
"ሃሳቡ ጥሩ ነበር፣ ግን ..." ነገሩ እንዳልጣማት ወዲያው ግልፅ ሆነ። ጸጋዬ ግን ሊያስጨርሳት አልፈለገም። ጓደኞቹን ጠቀሰና ሁሉም ተነስተው ማታ ያጠኑትን ያወርዱት ጀመር። በዚህም የክፍላቸው ተማሪዎችም ሆኑ መምህሯ መገረማቸው አልቀረም። ወዲያው አንዱን ተማሪ ልካ ባሏን አስጠራችው። እንደገባም፣
"ጸጋዬና ጓደኞቹ ግሩም ነገር አዘጋጅተውልናል" አለችው። እናም ጸጋዬን ጠቀሰችው። ቴያትራቸውን እንደገና ማቅረብ ያዙ። ግማሽ ያህሉን እንደዘለቁት፣ "ወይ ግሩም!" አለ ዲሬክተሩ። ባለቤቱ ትንሽ አቅጣጫ ብታሳያቸው ከዚህ የበለጠ ሊያደርጉት ይችላሉ ብሎም አሰበ። "ጃንሆይ የሚያዩት ተሆነ ትንሽ ቢደከምበት አይከፋም። ከሁሉ በፊት ግን አገረገዡን ማናገር አለብኝ። መቼም እሳቸው ሳያውቁ ጃንሆይ ፊት ምንም ነገር ማቅረብ አይቻልም።"
የእንግሊዝኛ መምህሯ ልጆቹን ለማዘጋጄት ድካሙን ተያያዘችው። ወደ አዳራሹ ወስዳም ታለማምዳቸው ገባች። ...
"ጸጋዬ፣ እስኪ እንደ ንጉሥ ሆነህ ልይህ፣ ቀና፣ ኮራ፣ ደራ ብለህ እንደዚህ .... እያንዳንዷ ቃል መሰማቷን ማረጋገጥ አለባችሁ።"
ዝግጅቱ ቀረበ። አጼ ኃይለ ሥላሴ በትርኢቱ መደሰታቸው አልቀረም፣ ተገርመዋልም። ጸጋዬንም በማለፊያ ፈገግታ ተመለከቱት። ከዚያ አንዱን አገልጋያቸውን ጠርተው የሆነ ነገር ሹክ አሉት። እሱም ወደ መድረኩ ተፈተለከና የህብረት ትምህርት መምህሩ አቶ እሸቴ ባዩና ሚስዝ ሃቺንግስ ባሉበት፣
"ጃንሆይ ምን እንዲያደርጉልህ ትፈልጋለህ?" ሲል ጸጋዬን ጠየቀው።
"ማ? እኔ?" ጸጋዬ መልሶ ጠየቀ።
"አዎ አንተ! ጃንሆይ ምን ቢያደርጉልህ ትወዳለህ?"
ምን እንደሚናገር ግራ ገባው። ከዚያ የህብረት ትምህርት መምህሩን "ምን ልበል?" ሲል ጠየቃቸው። አቶ እሸቴ ከማስታወሻ ደብተራቸው ላይ አንድ ገጽ ገንጥለው ''ሩቅ መንገድ እየተጓዙ ለሚማሩና ጦማቸውን ለሚውሉ የገጠር ልጆች ምግብ መግዣ የሚሆን አነስተኛ በጄት ቢመደብ" የሚል ጥያቄ በጽሑፍ አቀረቡ።
"በዚህ ትስማማለህ?" አለ አገልጋዩ።
"አዎ!" መለሰ ጸጋዬ። ንጉሡ ወረቀቷን መልከት ካደረጉ በኋላ፣
"ስለሌሎቹ ተማሪዎች አልጠየቅንህም፣ አንተ ምን ትፈልጋለህ ነው ያልንህ በለው" አሉት።
"ለያንዳንዱ ተማሪ የደንብ ልብስ ይሰጥልኝ ማለት ትችላለህ" አሉት አቶ እሸቴ።
"እሺ" አለ ጸጋዬ፡፤
"እሺ ምንድነው? ራስህ አትናገርም እንዴ?! ከአንተ አንደበት ነው መስማት የምፈልገው።" አለው አገልጋዩ።
"ለጃንሆ
ኢትዮሪካ, [4/19/2021 12:50 PM]
ይ የሚያደርሱልኝ ጥያቄ፣ የተማሪ ደንብ ልብስ ለሁሉም ተማሪዎች እንዲሰጥልኝ ነው።"
ከዚያ "ለያንዳንዱ ተማሪ አንድ አንድ የደንብ ልብስ እንደወደድከው፣ አብረውህ ትርኢት ላቀረቡት ለመላኩና ለዴሬሳ ሁለት ሁለት፣ ላንተ ደግሞ ሶስት እንዲሰጥ ጃንሆይ ፈቅደዋል።" ሲል አገልጋዩ ድምጹን ዘለግ አድርጎ ተናገረ።
"በል ጃንሆይን እጅ ንሳ"፣ አቶ እሸቴ ሹክ አሉት። አዳራሹ በጭብጨባ አስተጋባ።
በማግስቱ "ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ በአንድ የአምቦ አንደኛ ደረጃ ተማሪ የተዘጋጄ ቴያትር ተመለከቱ።" ተብሎ በጋዜጣ ወጣ። የጋዜጣው ቅጂዎች በዲሬክተሩ ቢሮ በሥርዓት ተቀምጠው ነበር። ያኔ ጸጋዬ ታዋቂ ሆነ። "ብራቮ ጸጋዬ!" አሉት መምህሮቹ ሳይቀሩ። "አኮራኸን! ማንነትህንም አሳይተሃል። ባለ ተሰጥዎ መሆንህንና ለትልቅ ቦታ ብቁነትህን አስመስክረሃል" ወዘተ. ውዳሴው ወረደለት። በሆነው ሁሉ፣ በተለይም ለንጉሡ የ"ምን ላድርግልህ?" ጥያቄ የሰጠው ምላሽ ያላስደሰተው አንድ ሰው ብቻ ነበር። አባቱ አቶ ገ/መድህን ቀዌሳ።
"መሬት ይስጡኝ ልትላቸው ይገባ ነበር። ያም ባይሆን ባንድ ደህና የመንግስት ሥራ ያስገቡህ ነበር። እስቲ ታላጣኸው ነገር ጨርቅ ትላለህ?! አሁን ይኼ እንጉሥ ፊት የሚቀርብ ጥያቄ ነው? ጅል!"
ይህን በዚሁ ልግታና ከስድስት ዓመታት በኋላ ወደተፈጠረ ሌላ አጋጣሚ ልውሰዳችሁ። አቶ ጸጋዬ በንግድ ሥራ ትምህርት ኮሌጅ የቤተ መጻሕፍት ክፍል ኃላፊ ነው። አጼ ኃይለሥላሴ ኮሌጁን ሊጎበኙ እቅድ ይዘዋል። ሽር ጉድ እየተባለም ነው። ጸጋዬ የመስተንግዶውን ኃላፊነት ከወሰዱት ውስጥ አንዱ ነበር። ንጉሡ ወደ ውስጥ እንደገቡ ዙሪያ ገባውን ቃኝተውና ጸጋዬን ለአፍታ ተመልክተው፣
"በቃ ተውከው ማለት ነው?" ሲሉ ይጠይቃሉ። እኔን ይሆን ያናገሩኝ? ጸጋዬ ተጠራጥሯል። መልስ የሚሰጥ ይጠፋና ሁሉም አይኖች እሱ ላይ ሲያርፉ ደግሞ ሃሳቡን እንደምንም አሰባስቦ፣
"እኔን ነው የጠየቁኝ፣ ጃንሆይ?" ይላል።
"አዎ፣ ሙያህን ተውከው ወይ?"
ጸጋዬ ገርሞትም አላባራ። ከስድስት ዓመታት በፊት ያዩትን ልጅ ዛሬም አልረሱትም ማለት ነው!
"ኧረ አልተውኩትም፣ ጃንሆይ" መለሰ ጸጋዬ።
"እስቲ ተዚያን ጊዜ ወዲህ የሠራኸውን ንገረን?"
"ቴያትሮችን ስጽፍና ሳዘጋጅ ነው የቆየሁ፣ እንደውም አንድ አዲስ ቴያትር ጽፌ መጨረሴ ነው።"
"የት አለ አዲሱ ቴያትርህ?"
"እማዶ ጠረጴዛዬ ውስጥ ነው፣ ጃንሆይ"
"በል አምጣና አንብብልን።" በእጁ የተጻፈውንና "የእሾህ አክሊል" የተሰኘውን ተውኔቱን ይዞ መጣና፣
"ባለ አምስት ትዕይንት ነው፣ ጃንሆይ። የትኛውን ላንብብልዎ?"
"የመጀመሪያውን ክፍል"
ጸጋዬ ማንበቡን ይቀጥላል። የንጉሡ አገልጋይ ወንበር አምጥቶ እንዲቀመጡ ቢጋብዛቸውም ያላዩ መስለው እንደቆሙ ማዳመጣቸውን ቀጠሉ። ለማሰቢያ ትንሽ ጊዜ የፈለጉ ይመስል አስተያየታቸውን ወዲያውኑ አልሰጡም። ከአፍታ በኋላ ግን ወደጸጋዬ ቀረብ ብለው፣
"ይኸ የመጀመሪያህ እንጂ የመጨረሻህ እንዳይሆን፣ ብዕርህን ችላ እንዳትለው" ብለው ከፈገግታ ጋር ትተውት ሄዱ። ጸጋዬ በህልሙ ይሁን በእውኑ ማመን ተሳነው።
ባለቅኔውና አጼ ኃይለሥላሴ ከዚያ ወዲያ ብዙ ጊዜ ተገናኝተዋል። ተወያይተዋል። ጸጋዬ ቅሬታውን ያቀረበባቸው አጋጣሚዎችም ነበሩ። ደረቱን ነፍቶ የቆመባቸው ወቅቶችም እንዲሁ። ትልቁና ደማቁ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን የሥነጽሑፍ ሽልማት የተቀበለበት ዕለት ነበር ልንል እንችላለን። በነገራችን ላይ የምትመለከቱት ጥበብ - "ቅኔና ባለቅኔ" - የሠዓሊ አወቀ ቀለሙ ፈጠራ ነው።