04/06/2026
የከሚሴ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን፣ በአዲሱ የተቋማዊ እሳቤ፣ በውስጥ ጥራት ማስጠበቅ (Quality Training) እንዲሁም በኢንስፔክሽንና ሱፐርቪዥን ሰነዶች ላይ ያተኮረ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ሰጥቷል።
ግንቦት 27 ቀን 2018 ዓ.ም በተካሄደው በዚህ የሥልጠና መድረክ ላይ፡
የኮሌጁ ከፍተኛ አመራሮችና የዘርፍ አስተባባሪዎች፣
የዞን የቴክኒክና ሙያ ተቋማት አግባብነትና ጥራት ቁጥጥር ቡድን መሪ፣
በከሚሴ ፖሊ ቴክኒክ ክላስተር ሥር የሚገኙት የባቲ እና የጨፋ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ተወካዮች እንዲሁም ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ተገኝተዋል።
በኮሌጁ የውስጥ ጥራት ማረጋገጥ ቡድን መሪ በኢንስትራክተር አህመድ እሸቴ ስልጠናው የተሰጠ ሲሆን በዚህ ሥልጠና ላይ ሰፊ ግንዛቤ የተፈጠረ ሲሆን፣ ተቋሙ በአሁኑ ወቅት ያሉበትን ዘርፈ-ብዙ ችግሮች በመቅረፍ የዓለም አቀፍ የደረጃ ማረጋገጫ (ISO Certified) ባለቤት ለመሆን መሥራት በሚቻልባቸው መንገዶች ላይ በጥልቀት ተመክሯል። ለዚህም አዲሱን የተቋማዊ እሳቤ መነሻ በማድረግ የወጡ ስታንዳርዶችን (ደረጃዎችን) ሙሉ በሙሉ ለማሟላት የተቀናጀ ጥረት መደረግ እንዳለበት ተመላክቷል።
የኮሌጁ ዲን አቶ ሙክታር ገዛኸኝ በሥልጠናው ማጠቃለያ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ሥልጠናው እንዲሁ በንድፈ-ሐሳብ ብቻ ተወስኖ መቅረት እንደሌለበት በጥብቅ አሳስበዋል።
“የሥልጠናው ዋነኛ ግብ ወደ ተግባር መለወጥ ነው” ያሉት አቶ ሙክታር፣ እያንዳንዱ የሥራ ኃላፊና ባለሙያ በተሰማራበት የሙያ መስክ አዲሱን እሳቤና የወጡ ስታንዳርዶችን መሠረት አድርጎ መፈጸም እንደሚጠበቅበት ገልጸዋል። ዲኑ አክለውም፣ ይህንን ዕቅድ ከዳር ለማድረስ ኮሌጁ ከወዲሁ አስፈላጊ የሆኑ መሠረተ-ልማቶችን ለማሟላት በቁርጠኝነት እንደሚሠራ አስታውቀዋል።